በቴሌኮም ማጭበርበር ድርጊት የተሳተፉ ግለሰቦች ላይ እርምጃ ተወሰደ

የኩባንያውን የሲስተም አጠቃቀም ፍቃድ ፖሊሲና የቴሌኮም ማጭበርበርን ለመከላከል የወጣውን ፖሊሲ በመጣስ ከ3ሺህ በላይ የቴሌኮም ጥቅል አገልግሎቶችን ለ2135 ደንበኞች በህገወጥ መልኩ በመሸጥ ላይ የተሳተፈ አንድ የተቋሙ ሠራተኛ እጅ ከፍንጅ ተይዟል፡፡ ግለሰቡ ይህን ህገወጥ ድርጊት የፈጸመው ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት በማሰብ ሲሆን የተቋሙ የሴኩሪቲ ቡድን ባደረገው ክትትል እጅ ከፍንጅ በመያዝ ለህግ አስከባሪ አካላት አስረክቧል፡፡ ከዚህ ህገወጥ ተግባር ጋር በተያያዘ ተገቢውን የአገልግሎት ክፍያ ለኢትዮ ቴሌኮም ሳይከፍሉ የቴሌኮም አገልግሎት የተመጠቀሙ 2135 ደንበኞች አገልግሎት እንዲቋረጥ ተደርጓል፡፡

የኩባንያው በህገወጥ ቴሌኮም ተግባር የሚሳተፉ ግለሰቦች እና ተቋማት ላይ ቀጣይነት ያለው ክትትል በማድረግና በማጣራት ተገቢውን እርምጃ የሚወሰድ ሲሆን በህገወጥ መንገድ የቴሌኮም አገልግሎት የሚጠቀሙ እና ለመጠቀም የሚሞክሩ ደንበኞችን አገልግሎት የሚያቋረጥ ሲሆን እንዲሁም ከህግ እና ከጸጥታ አካላት ጋር በመሆን በቀጣይ ህጋዊ እርምጃዎች የሚወሰድ ይሆናል፡፡

የቴሌኮም ማጭበርበር ተግባራትን በመከላከል ረገድ የህዝቡ ሚና ከፍተኛ በመሆኑ፣ የማጭበርበር ድርጊቶች ከገንዘብ ኪሳራ በተጨማሪ በሀገር ደህንነትና ኢኮኖሚ ላይ የሚያደርሰውን አደጋ በመገንዘብ እንዲሁም ኢትዮ ቴሌኮም የህዝብ ተቋም እንደመሆኑ የህዝብ ንብረት አላግባብ ተገቢውን ክፍያ ሳይከፍሉ የሚጠቀሙ ግለሰቦችና ተቋማት ሲገኙ ህዝቡ ለጸጥታና ለህግ አስከባሪ ተቋማት ጥቆማውን በማቅረብ ህገወጦችን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት የበኩሉን አስተዋጽዖ እንዲያበረክት ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡