ኢትዮ ቴሌኮም እና ሶምኬብል በአህጉራዊ የዲጂታል ትብብር እና ስትራቴጂያዊ አጋርነት ዙሪያ ተወያዩ
የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ ከሶምኬብል (Somcable) ሊቀመንበር መሐመድ ሰይድ ጉኡዲ እና ዋና ስራ አስፈጻሚ መሐመድ ኢብራሂም አህመድ ጋር በዓለም አቀፍ ዲጂታል እና ቴሌኮሙኒኬሽን ቢዝነስ ዘርፍ ድንበር ተሻጋሪ አጋርነት ለመመስረት ስትራቴጂያዊ ውይይት አካሄዱ።
ውይይቱ የዲጂታል መፍትሄዎችን በመጠቀም በውጭ ገበያዎች ያለውን የዕድገት አቅም ማፋጠን በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ሲሆን ዋና ስራ አስፈጻሚያችን የኩባንያውን የለውጥ ጉዞና ስትራቴጂያዊ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን ተግባራት በተመለከተ ገለጻ አድርገዋል።
ዋና ስራ አስፈጻሚያችን ኩባንያችን ድንበር ተሻጋሪ የዲጂታል መፍትሄዎችን ለማስፋፋት ያለውን ቁርጠኝነት ገልጸው፤ “ትብብር ለዲጂታል ዕድገት ወሳኝ ነው፤ ይህ አጋርነት የጋራ እሴት ለመፍጠርና በአፍሪካ የዲጂታል አቅምን ለማጎልበት ተሞክሯችንን እንድንጋራ ያስችለናል” ብለዋል፡፡
የሶምኬብል ሊቀመንበር “ከአፍሪካ ቀዳሚ ኦፕሬተሮች አንዱ ከሆነው ኩባንያ ጋር አጋር በመሆናችን ታላቅ ኩራት ይሰማናል” ያሉ ሲሆን የሶምኬብል ዋና ሥራ አስፈጻሚ በበኩላቸው፣ “ይህ ከሁለት ኩባንያዎች አጋርነት በላይ ነው፤ ይህም ቴክኖሎጂን በመጠቀም የሰውን ልጅ አቅም ለማሳደግ እና የበለጠ የተሳሰረችና የበለፀገች አፍሪካን ለመፍጠር ያለን ቁርጠኝነት ነው” ብለዋል።
በተጨማሪም ሁለቱ ኩባንያዎች አሁን ያለውን ዓለም አቀፍ የኢንተርኔት አቅም ለማሳደግ እና በሌሎች ስትራቴጂያዊ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመሥራት ተስማምተዋል።
ኢትዮ ቴሌኮም ያለውን ሰፊ መሠረተ ልማትና ቴክኒካዊ ብቃት በመጠቀም በዓለም አቀፍ የዲጂታል ገበያ አዳዲስ ዕድሎችን ለመክፈት የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ ይቀጥላል።




